በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ29ኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታ ባህርዳር ከተማ ሀዋሳ ከተማን 1 – 0 አሸንፏል ።
በጨዋታው በባህርዳር ከተማ በኩል በ28ኛው ሳምንት በሲዳማ ቡና 4 – 0 በተረቱበት ጨዋታ ላይ ከተጠቀሙት አሰላለፍ አራት ለውጦች በማድረግ በተስፋዬ ታምራት ፣ አለልኝ አዘነ ፣ ቻርለስ ሪባኑ እና ሀብታሙ ታደሰ ምትክ ፈቱዲን ጀማል ፣ ፉአድ ፈረጃ ፣ ፍቅረሚካኤል አለሙን እና አደም አባስን ተክተው ሲገቡ በሀዋሳ ከተማ በኩል ኢትዮ ኤሌክትሪክን በረቱበት ጨዋታ ላይ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ አንድ ለውጥ ብቻ በማድረግ ሰዒድ ሀሰንን በዳንኤል ደርቤ ተክተው ጨዋታውን መጀመር ችለዋል ።
በጨዋታው የመጀመሪያ ደቂቃዎች ላይ በኳስ ቁጥጥሩ ተሽለው የታዩ የመሰሉት ሀዋሳ ከተማዎች ቢመስሉም ቀስ በቀስ ጨዋታው ተመጣጣኝ የሆነ እንቅስቃሴ እስከ መጀመሪያው አጋማሽ መጠናቀቂያ ደቂቃዎች ድረስ አስመልክቶናል ።
- ማሰታውቂያ -
በአጋማሹ ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል ደርሶ ጥሩ የግብ ዕድሎች በመፍጠር የተሻሉ የነበሩት የጣና ሞገዶቹ በተደጋጋሚ አላዛር ማርቆስን የፈተኑ ሙከራዎችን ማድረግ ችለው ነበር ።
በሀዋሳ ከተማ በኩል የነበሩት የማጥቃት እንቅስቃሴዎች በተጋጣሚያቸው የኋላ ክፍል በቀላሉ ይነጠቁ ነበር ።
የጨዋታው ቀዳሚ ኢላማውን የጠበቀ የግብ ሙከራ በ9ኛው ደቂቃ ላይ የተደረገ ሲሆን መድኃኔ ብርሀኔ ከግራ መስመር ወደ ግብ ያሻማውን ኳስ ሙጂብ ቃሲም በግንባር ገጭቶ ወደ ግብ ቢልከውም በታፔ አላዝየር ተመልሷል ።
ከሶስት ደቂቃዎች በኋላም በሀዋሳ ከተማ በኩል አሊ ሱሌማን ከሳጥኑ ርቆ የወጣውን ግብ ጠባቂውን ፔፔ አላዝየርን አልፎ የነበረ ቢሆንም ፈቱዲን ጀማል ኳሱን ግብ ከመሆን አድኖታል ።
በባህርዳር ከተማ በኩል ማማዱ ሲዲቤ በ13ኛው ደቂቃ ላይ የቡድኑን ቀዳሚ ኢላማውን የጠበቀ የግብ ሙከራ ሲያደርግ በ15 እና 22ኛው ደቂቃ ላይ ፉአድ ፈረጃ እና ያብስራ ተስፋዬ ከቅጣት ምት በቀጥታ ወደግብ የመቷቸው ኳሶች በግብ ጠባቂው ተመልሰዋል ።
የጣና ሞገዶቹ ተደጋጋሚ የግብ ዕድሎች እየፈጠሩ በቀጠሉበት ደቂቃዎች ላይ ማማዱ ሲዲቤ ጥሩ አጋጣሚን አግኝቶ ሳይጠቀምበት ቀርቷል ።
አጥቂው ከረጅም ርቀት የተላከለትነ ኳስ ከግብ ጠባቂው ጋር ተገናኝቶ ከፍ አድርጎ ለማስቆጠር ያደረገው ጥረት ከግቡ አናት በላይ ወጥቷል ።
ሀዋሳ ከተማዎች የአጋማሹ መጠናቀቂያ ደቂቃዎች ላይ በኳስ ቁጥጥሩ የተሻሉ መስለው ቢታዩም የግብ ሙከራዎችን ከማድረግ አንፃር ግን ደካማ እንቅስቃሴን ነበርን ሲያሳዩ የነበሩት ።
የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቆ በተጨማሪ ደቂቃ ላይ ያብስራ ተስፋዬ ያስቆጠረው አስደናቂ ግብ ቡድኑን በ1 – 0 መሪነት ወደ እረፍት እንዲያመራ አስችሎታል ።
ማማዱ ሲዲቤ ከሳጥን ውጪ አክርሮ የመታውን ኳስ ግብ ጠባቂው አላዛር ማርቆስ ሲመልሰው ከሳጥን ውጪ ሆኖ ያገኘው 8 ቁጥር ለባሹ ያብስራ በግሩም ሁኔታ አስቆጥሮታል ።
የሁለተኛው አጋማሽ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሀይቆቹ የመጀመሪያ ደቂቃዎች ላይ ሀይቆቹ ተደጋጋሚ የማጥቃት እንቅስቃሴዎች በማድረግ ግብ ለማስቆጠር ጥረቶችን አድርገዋል ።
በ49 እና 52ኛው ደቂቃ ላይ ሰዒድ ሀሰን በግንባር ገጭቶ ለማስቆጠር ያደረጓቸው ጥረቶች ውጤታማ ሳይሆኑ ቀርተዋል ።
በ53ኛው ደቂቃ ላይም ሙጂብ ቃሲም ከሳጥን ውጪ ያደረገው የግብ ሙከራ በታፔ አላዝየር ተመልሷል ።
ሀይቆቹ ጫናቸውን አጠናክረው በመቀጠል የአቻነቱን ግብ ለማግኘት ቢጥሩም በጥሩ ንቃት ላይ የነበረው የባህርዳር ከተማ የኋላ መስመር ይህን የሚፈቅድ አልነበረም ። በ69ኛው ደቂቃ ላይ የመሀል ተከላካያቸው የሆነው በረከት ሳሙኤል በሁለተኛ ቢጫ ከሜዳ ተሰናብቷል ።
በቀጣዮቹ ደቂቃዎች ላይም በይበልጥ የጣና ሞገዶቹ የማጥቃት እንቅስቃሴ የታየበት ነበር ። በ71ኛው ደቂቃ ላይ ፍፁም ጥላሁን ከተከላካዮች ጀርባ የተጣለለትን ኳስ አግኝቶ አስቆጠረው ተብሎ ሲጠበቅ ሳይጠቀምበት ቀርቷል ።
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላም ፍራኦል መንግስቱ ከግራ መስመር ይዞ የገባውን ኳስ ወደ ግብ መምታት ችሎ የነበረ ቢሆንም አላዛር ማርቆስ ኳሱን ግብ ከመሆን አድኖታል ።
የጣና ሞገዶቹ በተደጋጋሚ በቀኝ መስመር በኩል ወደ ሀዋሳ ከተማ ሳጥን መግባት ቢችሉም አጋጣሚዎችን ሳይጠቀሙባቸው ቀርተዋል ።
በ85ኛው ደቂቃ ላይም ይሄነው የማታ ከፍቅረሚካኤል አለሙ ተቀብሎ ወደ ግብ የመታው ኳስ በግብ ጠባቂው ተመልሷል ።
በመጨረሻም ጨዋታው በባህርዳር ከተማ የ1 – 0 አሸናፊነት ተጠናቋል ።