አትሌት ተሰማ አብሽሮ
/የኬሮድ የስፖርትና የልማት ማህበር መስራችና ሰብሳቢ/
” የአንድነትና የትብብር እሴትን የሚያሳይ ውድድር እንደሚሆን እምነቴ ነው”
አቶ እንዳለ ስጦታው
/ የወልቂጤ ከተማ ከንቲባ/
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በ3ኛው የኬሮድ የጎዳና ላይ ሩጫ ከ1-6ኛ ደረጃ ያገኙ አትሌቶች የውጪ ዕድል ካገኙ ድጋፍ ለማድረግ መስማማቱ ተገለጸ።
- ማሰታውቂያ -
ነገ በወልቂጤ ከሚካሄደው የ3ኛው የኬሮድ የጎዳና ሩጫ ከመካሄዱ በዋዜማው ዛሬ ምሽት በሲራኖ ሆቴል በተሰጠው መግለጫ የኬሮድ የስፖርትና የልማት ማህበር መስራችና ሰብሳቢ የሆነው አትሌት ተሰማ አብሽሮ እንደተናገረው ” ከአትሌቲክስ ፌዴሬሽኑ ጋር ጥሩ ግንኙነት አለን። ስራ አስፈጻሚው ጨምሮ የምንፈልገውን ሁሉ እየደገፉን ነው በነሱ ደስተኞች ነን ነገር ግን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ውጤትም ችግርም አለው ችግሮቹ በሰላማዊ ውይይት መፍትሄ ቢያገኙ ደስተኞች ነን” ሲል ተናግሯል። አትሌት ተሰማ እንደገለጸው “ውድድሩ በጥሩ ፉክክር እንደሚካሄድ ተስፋ አደርጋለሁ በ3ኛው የኬሮድ
የጎዳና ላይ ሩጫ ከ1-6ኛ ደረጃ ያገኙ አትሌቶች የውጪ ዕድል ካገኙ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ድጋፍ ለማድረግ ፍቃደኛ ሆኗል ታላቁ ሩጫ ላይ ከ-10 ለወጡ አትሌቶች የድጋፍ ደብዳቤ ይሰጣል ከተጀመረ ገና ሶስተኛ አመቱን ለያዘው ለኛ ውድድር ድጋፍ ለመስጠት መታሰቡ በመሀላችን ያለውን ጥሩ ግንኙነት ያሳያል” በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል።
በነገው ሶስተኛው የኬሮድ የጎዳና ላይ ሩጫ ለመጀመሪያ ጊዜ የዊልቼር ውድድር በሁለቱም ጾታዎች መሃል እንደሚካሄድና በሁሉም ውድድር በሁለቱም ጾታ ላሸነፉት የገንዘብ ሽልማት የተዘጋጀ ሲሆን አንደኛ ለወጡት አትሌቶች የ75 ሺህ ብር በሽልማት መልክ መዘጋጀቱ ታውቋል።
በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ የተገኙት የወልቂጤ ከተማ ከንቲባ አቶ እንዳለ ስጦታው በበኩላቸው “የአንድነትና የትብብራችን እሴትን የሚያሳይ ውድድር እንደሚሆን እምነቴ ነው” ሲሉ ገልጸዋል። “ከተማችን ሰላም እንደሌላት ችግር እንደነበር ይናገሩ ለነበሩ ሰዎች መልስ ሰጥተናል። ከተማዋ አሁን 24 ሰአት ሰላም ያለባት ስልጡን ማህበረሰብ የሚገኝባት ከተማ መሆኗን አስመስክረናል የፖለቲካና የአመለካከት ልዩነት ቢኖርም ለሰላም ሲባል ግን ልዩነቱን ወደ ጎን በማለት አንድ ላይ የሚቆሙ መሆናቸውን አሳይተዋል” ያሉት ከንቲባው “ውድድሩ በሰላም ተጀምሮ በሰላም እንደ ሚፈጸም እንግዶቻችንም በሰላም ወደመጡበት እንደሚመለሱ ርግጠኛ ነን” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።