ሲዳማ ቡና ቴክኒካል ሪፖርት እንዲያቀርቡ ለአሰልጣኞቹ የሰጠው መመሪያ ባለመከበሩ ዋና አሰልጣኙን ስዩም ከበደና ምክትላቸውን አሰልጣኝ አረጋዊ ዘለለውን አግዷል።
ከክለቡ ታማኘ ምንጭ በተገኘ መረጃ የክለቡ አመራሮች አሰልጣኙ ትላንት ሀዋሳ በመገኘት ሪፖርት እንዲያደርግ ቢያዙትም አሞኛል ምክትሌን ልኬያለሁ ማለቱ ተሰምቷል …ያም ሆኖ ምክትሉም እንደተባለው ሪፖርት ባለማድረጉ አመራርቹ አሰልጣኞቹን ማገዳቸው ታውቋል።
በዝውውር መስኮቱ ጥሩ የተንቀሳቀሱት ሲዳማ ቡናዎች የሚፈለገውን ያህል ውጤታማ ያልሆኑ ሲሆን በተለይ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ አሸንፈው አንድ ጊዜ አቻ ወጥተው ሶስት ጊዜ ተሸንፈው በ4 ነጥብና 1 የግብ ዕዳ 11ኛ ደረጃ ላይ መገኘታቸው የክለቡን አመራሮች ማስከፋቱ ታውቋል። የክለቡ ቴክኒክ ኮሚቴ፣ የበረኛ አሰልጣኝና ቡድን መሪ ሪፖርት አቅርበው አሰልጣኞቹ ሪፖርት አለማቅረባቸው አመራሮቹ አሰልጣኞቹን እንዲያግዱ ማድረጉ ታውቋል።
በጉዳዩ ዙሪያ አሰልጣኝ ስዩም ከበደን ለማናገር ስልክ ደውለን የነበረ ሲሆን አሰልጣኙም ” ምቹ ቦታ ላይ ስላልሆንኩ ነዉ እደዉላለሁ” በማለት የጽሁፍ መልዕክት በመላኩ ምላሹን ማወቅ አልቻልንም።