በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት መርሀ ግብር የመጨረሻ ጨዋታ ሀድያ ሆሳዕና ነጥቡን ከመሪው ቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ያስተካከለበትን ውጤት አስመዝግቧል ።
በሀድያ ሆሳዕና በኩል በአምስተኛው ሳምንት ወላይታ ድቻን ባሸነፉበት ጨዋታ ላይ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ አንድ ለውጥ ብቻ አድርገው የገቡ ሲሆን ፀጋዬ ብርሀኑ ሰመረ ሀፍተይን ተክቶ የተሰለፈ ተጫዋች ነው ። በለገጣፎ ለገዳዲ በኩል ደግሞ በሳምንቱ በባህርዳር ከተማ በተረቱበት ጨዋታ ላይ ከተጠቀሙት ምርጥ 11 ሁለት ለውጦትችን በማድረግ ፍቅሩ አለማየሁን እና አንዋር አብዱልጀባር በበረከት ተሰማ እና ኦካይ ጁል ምትክ አሰልፈዋል ።
በመጀመሪያው አጋማሽ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሀድያ ሆሳዕና አንፃራዊ የበላይነት የነበራቸው ሲሆን በተለይም በሁለቱ ክንፎች በኩል የለገጣፎ ለገዳዲን መረብ ለማግኘት ጥረዋል ።
በለገጣፎ ለገዳዲ በኩል በቀጥተኛ ኳሶች ወደ ተገጣሚያቸው የግብ ክልሎች ለመድረስ የሞከሩ ሲሆን አጥቂው ካርሎስ ዳምጠውን ኢላማ ያደረጉ ተደጋጋሚ ኳሶችም ወደፊት ይላኩ ነበር ።
- ማሰታውቂያ -
በጨዋታው የመጀመሪያ የግብ ሙከራ በ2ኛው ደቂቃ ላይ ሲመዘገብ ለገጣፎ ለገዳዲዎች ያገኙትን የቅጣት ምት ኪሩቤል ወንድሙ በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ በግብ ጠባቂው ፔፔ ሰይዶ ተይዞበታል ።
ሀድያ ሆሳዕናዎች በጨዋታው የግብ ዕድል ለመፍጠር ተቸግረው የቆዩ ሲሆን ቀዳሚ የግብ ሙከራቸውን በ25ኛው ደቂቃ ላይ አድርገዋል ። ባዬ ገዛኸኝ በረጅም የደረሰውን ኳስ እየገፋ ሄድ አስቆጠረው ተብሎ ሲጠበቅ ከፍ አድርጎ ወደ ግብ የላከው ኳስ ከግቡ አናት በላይ ወጥቷል ።
በጨዋታው በሁለቱም በኩል መሪ ለመሆን ጥረቶችን ቢያሳዩም የግብ ሙከራዎች አለመኖራቸው ጨዋታውን ለዕይታ ሳቢ እንዳይሆን አድርጎታል ።
የመጀመሪያው አጋማሽ መጠናቀቂያ ደቂቃዎች ላይ ተፈራ አንለይ በረጅም የተላከለትን ኳስ የሀድያ ሆሳዕና ተከላካይን አልፎ ክግብ ጠባቂው ጋር መገናኘት ችሎ የነበረ ቢሆንም ዕድሉን ሳየጠቀምበት ቀርቷል ።
የመጀመሪያው አጋማሽም ያለ ግብ ፍፃሜውን አግኝቷል ።
በሁለተኛው አጋማሽ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በሁለቱም ተጋጣሚዎች በኩል ከጨዋታዉ ሶስት ነጥብ ይዘው ለመውጣት ጥረቶችን ያደረጉበት ነበር ። በአጋማሹ ምንም እንኳን በኳስ ቁጥጥሩ ረገድ ሀድያ ሆሳዕናች የተሻሉ የነበሩ ቢሆንም ወደ ግብ በመድረሱ ረገድ ለገጣፎ ለገዳዲዎች አንፃራዊ የበላይነት ነበራቸው ።
በ57ኛው ደቂቃ ላይ ከቅጣት ምት ወደ ግብ የተሻገረውን ኳስ መሀመድ አበራ በግንባር ገጭቶ ለማስቆጠር ያደረገው ጥረት ሳይሰምር ቀርቷል ።
ከአራት ደቂቃዎች በኋላ ካርሎስ ዳምጠው ጥሩ አቋቋም ላይ ሆኖ የደረሰውን ኳስ የመቆጣጠር ስህተቱ ታክሎበት በሳጥን ውስጥ ግብ ጠባቂውን አልፎ ለማስቆጠር ቢጥርሞ ሳይሳካለት ቀርቷል ። በአጋጣሚው ለገጣፎ ለገዳዲዎች የፍፁም ቅጣት ምት ይገባናል ቢሉም የዕለቱ የመሀል ዳኛ በዝምታ አልፈውታል ።
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ የሀድያ ሆሳዕናው ግብ ጠባቂ ኳስ በረጅም ለማውጣት ሲሞክር ካርሎስ ዳምጠው ነጥቆት የነበረ ቢሆንም አጥቂው ወርቃማውን አጋጣሚ አምክኖታል ።
ሀድያ ሆሳዕናዎች በ76ኛው ደቂቃ ላይ የጨዋታው የመጀመሪያ ኢላማውን የጠበቀ የግብ ሙከራ አድርገዋል ። አምበሉ ወርቅይታደስ አበበ ከሳጥን ውጪ አክርሮ ወደ ግብ የመታውን ኳስ ግብጠባቂው ወንድወሰን መልሶታል ።
መደበኛው የጨዋታ ክፍለጊዜ ተጠናቆ አምስት ያህል ደቂቃዎች የተጨመሩ ሲሆን በነዚልዠህ ደቂቃዎች ላይ የለገጣፎ ለገዳዲዎቹ ወንድወሰን ገረመው እና መዝገቡ ቶላ መጋጨታቸውን ተከትሎ መዝገቡ ጨዋታውን መቀጠል ሳይችል ቀርቷል ። የተጫዋቾች ቅያሪ አድርገው ጨርሰው የነበሩት ለገጣፎ ለገዳዲዎች ቀሪዎቹን ደቂቃዎች በጎዶሎ ለመጫወት ተገደዋል ።
ተጨማሪ ደቂቃዎች አልፈው የዳኛው የጨዋታ መጠናቀቂያ ፊሽካ ድምፅ ሲጠበቅ ሀድያ ሆሳዕናዎች ተቀይሮ በገባው ተመስገን ብርሀኑ ግብ ከጨዋታው ሶስት ነጥብ ይዘው ወጥተዋል ።
ሀድያ ሆሳዕናዎች ደሰታቸውን ከገለፁ በኋላ ከዳኛው ጋር አላስፈላጊ ንትርክ ውሰጥ ገብቶ የነበረው ግርማ በቀለ በቀጥታ የቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል።