* ክለቡ የተጣለበት ዕገዳ ተነስቷል….
* የቀድሞ አሰልጣኝ ፍሰሃ ጥዑመልሳንን ክፍያ ሲፈጽሙ ከአሰልጣኝ ዘማርያም ወ/ጊዮርጊስ ጋርም በሰላም ተለያይተዋል…
ከቀድሞ አሰልጣኝ ፍሰሃ ጥዑመልሳን ጋር ተያይዞ በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ዕገዳ ተጥሎባቸው የነበረው ድሬዳዋ ከተማ እግር ኳስ ቡድን አመራሮች የሚጠበቀውን ክፍያ በመፈጸማቸው ዕገዳቸው ተነስቶላቸዋል።
- ማሰታውቂያ -
ከፌዴሬሽኑ በተገኘ መረጃ መሠረት አሰልጣኝ ፍሰሃ ከአመት በፊት ድሬዳዋ ከተማን ውጤታማ አላደረክም ተብሎ ሲሰናበት ውል እያለው በመሆኑ የፌዴሬሽኑ የፍትህ አካላት የሚባሉት የዲሲፕሊንና የይግባኝ ሰሚ ኮሚቴ ወደስራ እንዲመልሱት ያ የማይሆን ከሆነ የውል ዘመኑን ክፍያ ከፍለው መለያየት ይችላሉ ቢሉም እስከቅርብ ጊዜ ድረስ ተፈጻሚ ሳይሆን ቀርቷል።
ይህን ተከትሎ የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽኑ ድሬዳዋ ከተማ ላይ በቅርቡ ያስተላለፈው ዕገዳ ውጤት ያመጣ ይመስላል ከዕገዳው ቀናቶች በኋላ ክለቡ ለአሰልጣኙ መክፈል የነበረበትን ወደ 300ሺህ ብር የሚጠጋ ክፍያ በመፈጸሙ ዕገዳው በትላንትናው ዕለት መነሳቱን ከፌዴሬሽኑ የተገኘው መረጃ ያስረዳል።
በሌላ በኩል ከፍተኛ ውዝግብ ላይ የነበሩት ድሬዳዋ ከተማና አሰልጣኝ ዘማርያም ወ/ጊዮርጊስ በስምምነት መለያየታቸው ተሰምቷል። ባለፈው ሳምንት የዲሲፕሊን ኮሚቴ አሰልጣኙ የተሰናበተው ውል እያለው ነው ወደቦታው ይመለስ አሊያም በውሉ ስር ያለው የደመወዝ ክፍያው ተፈጽሞለት መለያየት ይችላሉ የሚል ውሳኔ አሳልፎ የነበረ ሲሆን ክለቡ ይግባኝ በመጠየቁ የይግባኝ ሰሚ ኮሚቴ ምላሽ እየተጠበቀ ባለበት ሰዓት ነው ሁለቱ ወገኖች ስምምነት ላይ መድረሳቸው የተሰማው ተብሏል።
አሰልጣኝ ዘማሪያም ከክለቡ ከፍተኛ የቦርድ አመራር አካላትና ከአሸማጋዮች ጋር ተደጋጋሚ ውይይት ካደረገ በኋላ መስማማታቸው የተነገረ ሲሆን የክለቡ ስራ አስኪያጅ ፌዴሬሽን ጽ/ቤት በመገኘት ስምምነታቸውን በፊርማቸው በማጽደቅ መለያየታቸው ይፋ ሆኗል። የሁለቱ ወገኖች ስምምነትን ተከትሎ ጽ/ቤቱ ለይግባኝ ሰሚ ኮሚቴ ደብዳቤ በመጻፍ የአሰልጣኝ ዘማሪያም ክስ እንዲቋረጥ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል።
ስምምነቱ የፌዴሬሽኑ ዋና ጸሃፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን አሰልጣኝ ዘማሪያም ወ/ጊዮርጊስ እያሉ አሰልጣኝ ሳምሶን አየለ ለድሬዳዋ ከተማ እንዲፈርሙ የፈቀዱበት ውሳኔያቸው ይፈጥር የነበረውን ከፍተኛ ውዝግብ ያስቀረ ሆኗል። በተቃራኒው አዲሱ አሰልጣኝ ሳምሶንም በተረጋጋ ሁኔታ በነጻነት ስራቸውን እንዲሰሩ የተመቻቸ ዕድል እንደሚፈጥርም ይታመናል።