ከሀምሌ 10 ጀምሮ በባህርዳር አለም አቀፍ ስታዲየም ለሚጀምረዉ የሴካፋ ከ 23 ዓመት በታች ውድድር የምድብ ድልድል ዕጣ ዛሬ ከሰዓት እንደሚወጣ ይፋ ሆኗል።
ሴካፋ ባሳወቀው መሰረት በምድብ ድልድሉ ላይ ዘጠኝ ሀገራት መኖራቸውን በመግለፅ ዩጋንዳ ፣ ኤርትራ ፣ ቡሩንዲ ፣ ኢትዮጵያ ፣ ጅቡቲ ፣ ደቡብ ሱዳን ፣ ኬንያ ፣ ታንዛኒያ እና ተጋባዧ ዲሞክራቲክ ኮንጎ መሆናቸውን ተነግሯል ።
ለ41ኛው የምስራቅ እና መካከለኛው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ከሰኔ የመጀመሪያ ቀናት አንስቶ ሲዘጋጅ የነበረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንም ከትላንት ወዲያ አመሻሽ ላይ ውድድሩ ወደሚደረግበት ባህር ዳር ከተማ አቅንቷል።ብሔራዊ ቡድኑ ልምምዶችን ከማድረጉ በተጨማሪ ከሀገር ውስጥ ክለቦች ጋር የአቋም መለኪያ ጨዋታዎችን ሲያደርግ ነበር። ልዑካን ቡድኑም መቀመጫቸዉን በብሉ ናይል (አቫንቲ) ሆቴል ማድረጋቸው ተሰምቷል።
በአሠልጣኝ ውበቱ አባተ የሚመራው የኢትዮጵያ ከ23 አመት በታች ብሔራዊ ቡድን በበኩሉ ስንታየሁ መንግስቱን ከስብስባቸው ቀንሰዉ ፤ በምትኩ አሠልጣኙ ለወልቂጤ ከተማው የመስመር ተከላካይ ረመዳን የሱፍ ጥሪ አቅርበዉለታል። ለክለቡ ወልቂጤ ከተማ ግልጋሎት ሲሰጥ የቆየዉ ተጫዋቹ ዛሬ ብሔራዊ ቡድኑን እንደሚቀላቀል ተጠቁሟል። ዉድድሩ የፊታችን ቅዳሜ በባህርዳር አለም አቀፍ ስታዲየም የሚጀምር ይሆናል።