የመርሐግብሩ ዉጤት ወሳኝነቱ ከፍ ባለዉ ጨዋታ ሁለቱም ቡድኖች በተመጣጣኝ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ የመጀመሪያዎቹን ደቂቃዎች መንቀሳቀስ ችለዉ የነበረ ቢሆንም በሂደት ግን የጣና ሞገዶቹ የጨዋታውን እንቅስቃሴ የበላይነት በመዉሰድ ጫና ፈጥረዉ ለመጫወት ሲሞክሩ ተስተውሏል።
ያን ያህል በሙከራ የታጀበ ጠዋታ ነበር ለማለት ባያስደፍርም ገና በጨዋታዉ መባቻ ላይ አዲስ አዳጊዎቹ ጥሩ ሙከራ ማድረግ ችለዉ ነበር በዚህም በ10ኛዉ ደቂቃ ላይ ከቀኝ መስመር የተሻገረለትን ኳስ ያብቃል ፈረጃ በጭንቅላ ገጭቶ ወደ ግብ ሲሞክር የጣና ሞገዶቹ ግብ ጠባቂ ተቆጣጥሮታል።
የጨዋታው ደቂቃ እየገፋ በመጣ ቁጥር የጣና ሞገዶቹን የማጥቃት እንቅስቃሴ መቋቋም ያቃታቸው የሚመስሉት ለገጣፎዎች ወደ ኋላ አፈግፍገዉ በመልሶ ማጥቃት ለመጫወት ሲጥሩ ተስተዉሏል። በ27ኛዉ ደቂቃ ላይ ከሔኖክ ኢሳያስ የተቀበለዉን ኳስ አደም አባስ ለአጥቂዉ ኦሴ ማዉሊ አቀብሎት አጥቂዉ በድንቅ ብቃት ወደ ግብነት ቀይሮ የጣና ሞገዶቹን መሪ ማድረግ ችሏል።
ግብ ከተቆጠረባቸው በኋላ ወደ ጨዋታዉ ለመመለስ በቻሉት መጠን መንቀሳቀስ የጀመሩት ለገጣፎዎቹ በ37ኛዉ ደቂቃ ላይ ድንቅ ለግብ የቀረበን ሙከራ ማድረግ ችሏል። በዚህም የግራ መስመር ተጫዋቹ አስናቀ ተስፋየ የተገኘዉን የቅጣት ምት ኳስ ቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም የግብ ዘቡ ታፔ አልዛየር ተቆጣጥሮታል።
ከዕረፍት መልስ በባህርዳር ከተማ የኳስ ቁጥጥር የበላይነት በቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ በ54ኛዉ ደቂቃ ላይ ድንቅ ሙከራ በጣና ሞገዶቹ በኩል ተመልክተናል። በዚህም የመስመር ተጫዋቹ ፉአድ ፈረጃ ቀጥታ ወደ ግብ የመታዉን የቅጣት ምት ኳስ ግብ ጠባቂዉ ወንድወሰን ሲመልሰዉ አቅራቢያው የነበረዉ ማሊያው አጥቂ ኦሴ ማዉሊ ቢሞክርም በድጋሚ የግብ ዘቡ ተቆጣጥሮታል።
አሁንም እንደ መጀመሪያዉ አጋማሽ በመልሶ ማጥቃት አጥቂዉን ካርሎስ ዳምጠዉን ያማከሉ ኳሶችን በመጣል ለመጫወት ሲጥሩ የነበሩት ለገጣፎዎች በተቃራኒው ሁለተኛ ግብ አስተናግደዋል። በዚህም በ65ኛዉ ደቂቃ ላይ አደም አባስ ከተከላካዮች ጋር ታግሎ ያቀበለዉን ኳስ የመስመር ተጫዋቹ ፉአድ ፈረጃ ወደ ግብነት በመቀየር የጣና ሞገዶቹን መሪነት ወደ ሁለት ለዜሮ ከፍ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ሁለተኛ ግብ ካስተናገዱ በኋላ በጥቂቱም ቢሆን መነቃቃት ይታይባቸው የነበሩት ለገጣፎዎች በመጠኑም ቢሆን የጨዋታወሐ መገባደጃ ወቅት አልፎ አልፎ ሙከራን ማድረግ ቢችሉም ዉጥናቸዉ ሰምሮ ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ጨዋታዉ በባህርዳር ከተማ 2ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።