በአሰልጣኝ ፓውሎስ ማንጎ እየተመሩ ደካማ ጅማሮን ቢያሳዩም ከጨዋታ ጨዋታ መሻሻሎችን በማሳየት ጠንካራ ተፎካካሪ እየሆኑ የሚገኙት ጅፋራውያን በአዲሱ ስታዲየማቸው ያለመሸነፍ ጉዟቸው አስቀጥለዋል ::
ዘጠኝ ሰአት በጀመረው በዚህ መርሀ ግብር በመጀመሪያው አጋማሽ ተመጣጣኝ ፉክክር ሲታይበት በወልቂጤዎች ተደጋጋሚ ጥፋቶች ጨዋታው በተደጋጋሚ ሲቋረጥ ተስተውሏል ::
በጨዋታው የመጀመሪያ አስር ደቂቃዎች ላይ ሁለቱም ቡድኖች ወደ ግብ መድረስ ቢችሉም ግብ ሊያስተናግዱ ግን አልቻሉም ::
- ማሰታውቂያ -
በተለይም ክትፎዎቹ ተጭነው ለመጫወት ቢሞክሩም በፊት መስመር ላይ ያለባቸው ክፍተት ግብ እንዳያስቆጥሩ ሲያደርጋቸው ታይቷል ::
የመጀመሪያው አጋማሽ ምንም ጎል ሳያስተናግድ ሲጠናቀቅ የሁለተኛው አጋማሽ በጅማ አባ ጅፋር የማጥቃት ጫናዎች ለመካሄድ ችሏል ::
በተለይም የተጫዋቾች ቅያሪን ካደረጉ በኋላ አጥቅተው የተጫወቱት ጅማዎች በንጋቱ ገብረ ስላሴ አማካኝነት መሪ መሆን የቻሉበትን ጎል አስቆጥረዋል ::
ከጎሉ መቆጠር በኋላ ወልቂጤዎች ወደ ጎል መቅረብ ቢችሉም ሰኢድ ሀብታሙን በመተካት የተሰለፈው ግብ ጠባቂው ሙንታሪ ተደጋጋሚ ሙከራዎችን ሲያድን አምሽቷል ::
የጨዋታው ክፍለ ጊዜ በዚህ ውጤት ሲጠናቀቅ ጅማ አባ ጅፋር በሊጉ በአስር ነጥቦች በአምስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ሲችሉ ሽንፈት ያስተናገዱት ክትፎዎቹ በስምንት ነጥቦች ወደ አስራ ሁለተኛ ለመውረድ ተገደዋል።
ሊጉን ወልዋሎ አ.ዩ. በ14 ነጥቦች ሲመራ መቐለ 70 እ. እና ፋሲል ከተማ በቅደም ተከተል በ13 እና በ12 ነጥቦች 2ኛ እና 3ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። የኮከብ ግብ አግቢነቱን ደግሞ የፋሲል ከነማው ሙጂብ ቃሲም በ7 ግቦች ቀዳሚ ሲሆን የባህርዳር ከነማው ፍፁም ዓለሙ በ6 እንዲሁም የመቐለ 70 እ. አማኑኤል ገ/ሚካኤል በ5ግቦች ተከታዩን ደረጃ ይዘዋል።