የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአንደኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች በዛሬው ዕለት ሲደረጉ ስድስት ግቦች በተስተናገዱበት ጨዋታ ፋሲል ከነማነሠ ሀዋሳ ከተማ ነጥብ ተጋርተዋል ።
በጨዋታው በአሰልጣኝ ውበቱ አባተ በሚመራው ፋሲል ከነማ በኩል ሚኬል ሳማኪ ፣ መናፍ ዐወል ፣ ምኞት ደበበ ፣ ዮናታን ፍስሀ ፣ ዓለምብርሀን ይግዛው ፣ ሱራፌል ዳኛቸው ፣ ሽመክት ጉግሳ ፣ ይሁን እንደሻው ፣ ጋቶች ፓኖም ፣ አማኑኤል ገብረሚካኤል እና ጌታነህ ከበደ በምርጥ 11 ተካተዋል ።
እንዲሁም በአሰልጣኝ ዘርዓይ ሙሉ በሚመራው ሀዋሳ ከተማ በኩል ፅዮን መርዕድ ፣ መድኃኔ ብርሀኔ ፣ ሰለሞን ወዴሳ ፣ ሚሊዮን ሰለሞን ፣ እንየው ካሳሁን ፣ ታፈሰ ሰለሞን ፣ አብዱልባሲጥ ከማል ፣ አማኑኤል ጎበና ፣ ሙጂብ ቃሲም ፣ እዮብ አለማየሁ ፣ አሊ ሱሌማን በመጀመሪያው አሰላለፍ የተካተቱ ተጫዋቾች ናቸው ።
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ ፋሲል ከነማ ተሽሎ በታዩበት ጨዋታ ግብ በማስቆጠሩ ቀዳሚ መሆን ችለዋል ።
- ማሰታውቂያ -
በጨዋታው 9ኛ ደቂቃ ላይ ሱራፌል ዳኛ ከርቀት ያገኘውን የቅጣት ምት ለቡድን አጋሮቹ ያሻማል ተብሎ ሲጠበቅ በቀጥታ ወደ ግብ በመምታት ከመረብ አሳርፎታል ።
በማጥቃት እንቅስቃሴ የተሻሉ የነበሩት አፄዎቹ ከመጀመሪያው ግብ መቆጠር በኋላ ጥሩ ጥሩ የግብ ዕድሎች ለማግኘት ችለዋል ።
በ13ኛው ደቂቃ ላይ ሽመክት ጉግሳ ከሚሊዮን ሰለሞን የነጠቀውን ኳስ ለጌታነህ ከበደ ማቀበል ቢችልም አጥቂው ጌታነህ ከበደ ያገኘውን አጋጣሚ ሳይጠቀምበት ቀርቷል ።
በሀዋሳ ከተማ በኩልም በተወሰኑ አጋጣሚዎች የፋሲል ከተማን የኋላ ክፍል ሰብረው በመግባት የግብ ዕድሎች ለመፍጠር ቢጥሩም በቀላሉ ሊያደርጉት አልቻሉም ።
በጨዋታው 20ኛው ደቂቃ ላይ ጌታነህ ከበደ ለሱራፌል ዳኛቸው አቀብሎ ወደ ሳጥን ሲገባ ኳሱን ከሱራፌል የደረሰው ሽመክት ወደ መሀል ቀንሶት ጌታነህ ከበደ ኳስና መረብን አገናኝቷል ።
ሀይቆቹ በ36ኛው ደቂቃ ላይ የጨዋታውን የመጀመሪያ የግብ ዕድል መፍጠር የቻሉ ሲሆን ታፈሰ ሰለሞን ወደ ሳጥን ያሻገረውን ኳስ ሙጂብ ቃሲም በግንባር ገጭቶ ወደ ግብ ልኮት ለጥቂት ወደ ውጪ ወጥቶበታል ።
የጨዋታው የመጀመሪያው አጋማሽ በፋሲል ከነማ የ2 – 0 መሪነት ሲጠናቅቅ በሁለተኛው አጋማሽ ግን የተለየ መልክን በመያዝ ነበር ።
ሀዋሳ ከተማዎች በሁለተኛው አጋማሽ ግብ ለማስቆጠር የፈጀባቸው 24 ሰከንዶች ብቻ ነበር ።
ከግብ ጠባቂው ፅዮን መርዕድ የተነሳውን ኳስ የቀድሞው የፋሲል ከነማ ተጫዋች ታፈሰ ሰለሞን ከመረብ ላይ አሳርፎታል ።
ከአራት ደቂቃዎች በኋላ ጌታነህ ከበደ ጥሩ የግብ ዕድል አግኝቶ ወደ ግብ የመታው ኳስ በፅዮን መርዕድ ተይዞበታል ።
ጨዋታው 55ኛው ደቂቃ ላይ ሲደርስ አሊ ሱሌማን ከመጀመሪያውን ግብ አስቆጣሪው ታፈሰ ሰለሞን የደረሰውን ኳስ በግሩም ሁኔታ የግብ ጠባቂውን መውጣት ተመልክቶ ከመረብ አሳርፎታል ።
ጫና ማሳደራቸው የቀጠሉት ሀዋሳ ከተማዎች በ80ኛው ደቂቃ ላይ ከ2 – 0 መመራት ወደ 3 – 2 መሪነት የተሸጋገሩበትን ጎል አስቆጥረዋል ።
የሁለተኛው ግብ አስቆጣሪ አሊ ሱሌማን ከቅጣት ምት ያሻገረውን ኳስ ተከላካዩ በረከት ሳሙኤል በሳማኪ ሚኬል መረብ ላይ አስቆጥሮታል።
ሶስተኛውን ግብ ካስተናገዱ በኋላ የሀዋሳ ከተማን የኋላ መስመር ደጋግመው የፈተሹት ፋሲል ከነማዎች አቻ የሆኑበትን ግብ በ85ኛው ደቂቃ ላይ አስቆጥረዋል ።
የመጀመሪያውን ግብ በቅጣት ምት ያስቆጠረው ሱራፌል ዳኛቸው በድጋሚ ከቅጣት ምት ለራሱ ሁለተኛ ለቡድኑ ደግሞ ሶስተኛውን ግብ ከመረብ አሳርፏል ።
የጨዋታው መደበኛ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በተጨመሩት 4 ደቂቃዎች ላይ በረከት ሳሙኤል በአለምብርሀን ይግዛው ላይ በሰራው ጥፋት የማስጠንቀቂያ የቢጫ ካርድ ሲመለከት ከዕለቱ የመሀል ዳኛ ባህሩ ተካ ጋር በነበረው ንግግር በሁለተኛ የቢጫ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል ።
በመጨረሻም አዝናኛ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ ከስድስት ግቦች ጋር ያስተናገደው ጨዋታው በ3 – 3 ውጤት ተጠናቋል ።
በሁለተኛ ሳምንት ጨዋታዎች በመጪው አርብ ጥቅምት 2 በ12:00 ፋሲል ከነማ ከኢትዮጵያ መድኅን እንዲሁም እሁድ ጥቅምት 4 በ12:00 ሀዋሳ ከተማ ከሻሸመኔ ከተማ ይጫወታሉ ።