ወደ 52 ኢንተርሚዲየሪዎች ከፌዴሬሽንና ከፊፋ ላይሰንስ ቢወስዱም ገበያው ግን ያጠገበው ጥቂቶችን ነው፡፡ ህገወጦች ናቸው ከሚባሉት ፍቃድ ከሌላቸው በላይ እነዚህ መሃል ያለው ፍትጊያ ይበልጣል፡፡ 20 ሺህ ብር ለኢንሹራንስና ሌሎች ክፍያዎች ከከፈሉት ሰርተው ዋናቸውን መመለስ ያልቻሉት ይበዛሉ…ፌዴሬሽኑ ውል ለማደስ የክፍያ ጊዜ አሳውቆ ክፈሉ ማለቱ ሊስተካከሉ የሚገባቸው ሳይስተካከሉ በመሆኑ ያመጣውን ቅሬታ ከግምት አስገብቶ የክፍያውን ጉዳይ ለጊዜው ማራዘሙን አስታውቋል፡፡ ክፍያው የግድ ቢሆንም የውድድሩ ሜዳ እኩል ባልሆነበት …ያሉት የስነ ምግባር ጥሰቶች ባልተወገዱበት የሃይል ሚዛኑን እንዳያዛባው ተሰግቷል፡፡ ተጨዋቹ በራሱ ምርጫ ሳይሆን በክለብ አመራሮች በዘርና በአካባቢነት ስሜት እንዲሁም ከአሰልጣኝ ጋር በጥቅም ተሳስረው የሚሰሩ ወኪሎች ባለበት ብዙሃኑ ወኪልና ተጨዋች ተጎጂ ይሆናሉ ፡፡ ህጉ ተጨዋቹ የሚሰራለትን በራሱ ፈቃድ እንዲመርጥ ቢፈቅድም የአገራችን አብዛኛው አሰልጣኞችና አመራሮች በጥቅም ተሳስረዋል ተብሎ ስሞታ ይቀርብባቸዋል፡፡ አሁን ተጨዋቹ በክፍያ ቢጣላ ወኪሉ ለማን ሊቆም ነው? ለወኪሉ ተጨዋቹ ይከፍላል የሚጠቀሙት ግን ሌሎች… ተጨዋቾች በእንትና በኩል ካልመጣችሁ ተብለው ወኪል የቀየሩ በተለይ ሲኒየሮች ሲሆኑ ያማል፡፡ ለሚዲያ አቀርብልሃለሁ…ለብሄራዊ ቡድኑ አስመርጥሃለሁ ወዘተ በሆኑ የውሸት ድለላዎች ወኪል በቀየሩ ደግሞ እፍረቱ ይብሳል፡፡ ተጨዋቹ ለፍትህ አይቆምም ይፈራል ለዚህ ነው እንደተፈለገ ሲያገላብጡት የሚገላበጠው ተብሎም ይተቻል፡፡
ፌዴሬሽኑ መሠል ችግሮችና ሙስናዎች በተንሰራፋበት የዝውውር ሂደት ዙሪያ ፈቃድ የሰጣቸውን ህጋዊ ወኪሎችን/ብዛት ያላቸውና በደንብ የሸቀሉ እንዲሁም በመድረኩ ሙስና ውስጥ ማሸነፍ ያልቻሉና ያልሸቀሉ ጥቂቶች/ ለውይይት እንደሚጠራ አሳውቋል፡፡ በዘርፉ የተንሰራፋውን ሙስናና ችግሮች አጥርቶ የስራ መመሪያ ከሰጠ በኋላ የውል ማደሱ ሂደት እንደሚቀጥል አሳውቋል፡፡
በነገራችን ላይ አዲስ የተቋቋመው የኢንተርሚዲየሪዎች ማህበር አመራሮች “እጃችን ላይ መረጃና ማስረጃ ስላለ ወደ ህጋዊ መስመር የማይመለሱትን ወደ ህግ እንወስዳቸዋለን” ማለታቸው 2013 ዘራፊ አሰልጣኞች አመራሮችና ወኪሎች የሚጋለጡበት እንደሚሆን ተስፋ አደርጋለሁ….